Theme images by kelvinjay. Powered by Blogger.

Slider

ESAT

Ethiopian News

Movies

Drama

Sport

Opinion

History

የኔስ ሔዋን ~ ክፍል - 2 [ከአስጌ]



የኔስ ሔዋን ~ ክፍል - 2 [ከአስጌ]

7ኛ ክፍል ግን አንድ አዲስ ነገር ተከሰተ። የ7ኛ ክፍል ትምህርት ከጀመርን 2ወራትን አሳልፈናል። በነዚህ የሁለት ወራት የትምህርት ጊዜ ውስጥ በጓደኛየ አማካኝነት አንዲት ሴት ልጅ ጋ ተዋውቄ ነበር።  

ልጅቱም በተከታታይ ወደኔ መመላለስዋንና በወሬ ማጥመድዋን ተያይዘዋለች። "ትሳፋርይዋ አድማጬ በጉጉት እየተከታተለች እሽ ከዛስ አለች።" ከዛማ አንድ ቀን በእረፍት ላይ ክላስ መጣችና የሆነ ነገር እንደሆነች መናገር ፈለገችና መልሳ የአማረኛ ደብተሬን ወስዳ በቤት አመጠዋለሁ ብላ ከተቀመጥንበት ተነስታ ወደ ክላስዋ ሄደች። 

እኔም የልጅቱ ሁኔታ ግራ ቢያጋባኝም ግን ምን እንደፈለገች መገመትና ማወቅ አልቻልኩም ነበር። ከእረፍት በውሀላ ያለውን ይ3ክፍለ ጊዜ ና የ2ሰአት ቆይታየ እጅግ ከባድ ነበር። እንዲያውም ምን ተከሰተ መሰለሽ እ ምን ተከሰት አለች በጉጉት የተፈጠረውን ለመስማት

ከእረፍት በውሀላ ያለውን ክፍለ ጊዜ መማር አቅቶኝ በጉጉት አንዴ መነሳት አንዴ መቀመጥ ብቻ ግን ምን እንደሆነች ስላላወኩ እጅግ ጓጉቼ ነበር። እናም በርበሩን መመልከቴን ተያያዝኩት። 

ከዛማ የ4ኛው ክፍለ ጊዜ ሲያልቅ መምህር ተከትየ ስወጣ መምህሩም ለምን ተከትለኸኝ ወጣህ በሚል ሰበብ ወደ ቢሮ ወሰደኝ። መምህሩና ዳይሬክተሩ አስተያየታቸው ሲያስፈራ ብታይ በስማም ገደል ይከታሉ።  

እኔም በመምህሩ ሁኔታ እየተገምኩ ዳይሬክተራችን ምን እንዳጠፋው ጠየቀ። መምህር ስንታየሁም ተቻኮለና እኔ እዛ ክላስ እምገባው እሱ ሲወጣ ነው ካለዛ አይሆንም እሽ እሱ ባለበት ክፍል አላስተምርም ብሎ ብሶቱን ተናገረ። 

እና ዳይሬክተሩ ምን አለህ ባክህ አለች የታሪኬ ተከታታይ ተሳፋሪዋ ጓደኛየ ዳይሬክተሩም እሽ መምህር ስንታየሁ ልጁን እኛ እናስተካክለዋለን እሽ አለና ወደኔ ተመለከተ። ከዛ እኔም ቀበል አደረኩና በፍጥነት አይ ጋሼ ይሄን ያክል ያስቼገርኩህ አልመሰለኝም ነበር።  

አልኩና እግሩ ስር ተደፍቼ ይቅርታ ጠየኩት። እና ይቅርታ አደረገልህ አለች ተሳፋርዋ ጓደኛየ። ከዛማ መምህሩና ዳይሬክተሩ እርስ በርስ ሲፈጠጡ በጨረፍታ ተመለከትኳቼው። መምህሩም በይሉኝታና በሼም ሳይፈልግ በግድ ይቅርታ አደረግልኝና ተለያየን። እኔም በሱ ፔሬድ በድጋሜ ላልረብሽና ላልፎርፍ ለራሴ ቃል ገባው። 

ይትምህርቱ ሰአት ሊያልቅ የቀረን 15 ደቂቃ ብቻ ነው። ይህችን 15 ደቂቃ እንዴት ላሳልፋት በጣም ሲበዛ እረዘመችብኝ። ማለት በቃ ሀሳቤ ሁሉ ልጅትዋ ጋር ሆነ ምን ሆና ይሄን፣ ምን አርጌያት ይሆን ፤ብቻ አላቅም በውስጤ ብዙ ሀሳቦችን እያመላለስኪ 15 ደቂቃው አልቆ ወደ ቤት እንድንሄድ የሚያበስረን ደወል ተደወለ እኔም ክፍል ገብቼ ፖርሳየን ይዤ ስወጣ ከርቀት ተመለከትኳት።  

ለመውጣት እየተዘጋጀው አስዋን መመልከቴን አላቆምኩም ነበር ግን ምንም አዲስ ነገር አላየሁም ያው ደብተሬን ይዛው መጣችና ከደብተሬ ውስጥ የሆነ ነገር ከትታ ሰጠችኝ። እኔም ምንድነው ብየ ጠየኩአት። 

መልሳ ቤት ብቻህን ሁነህ እየው አለችኝ። ተሳፋሪዋ ጓደኛየም እና ምንድነው የሰጠችህ አለች ለመስማት በመጓጓት። ያው ወደቤት እየተጣደፍኩ ሄድኩና ዶርሜ ገብቼ ፖርሳየን ከፈትኩና ያንን ደብተር አወጣውት.. .........

ክፍል 3 ይቀጥላል


የኔስ ሔዋን ~ ክፍል - 1 [ከአስጌ]

የኔስ ሔዋን ~ ክፍል - 1

ከባህር ዳር ወደ አዲስ አበባ በመብረር ላይ ባለው የህዝብ ማመላለሻ መኪና ውስጥ ገብተን (ተሳፍረን) መጓዝ ከጀመትን 1፡00 ይሆነናል።  


በጉዞው ውስጥ ሰወች የየራሳቸውን ምርጫ ተጠቅመው አንዳንዶቹ ስልካቼው ጋ ይታገላሉ። ሌሎች ደግሞ መፅሀፍትን ያያሉ። አንቻንዶች ደግሞ ተኝተዋል። 

ሰወችን ተዛውሬ ከተመለከትኩ በውሀላ እኔም የራሴን መደበርያ በመፈለግ ወደ ዋሌት ፖርሳየ እጀን በመላክ ከሆዋላ ኪሴችመዘዝ አድርጌ አውጥቼ ፎቶ ማየትና ማገላበጥ ስጀምር ከጎኔ የተቀመጠች አንድ እህቴ ( ተሳፋርይዋ ሴት ማለቴ ነው ) የማገላብጣቼውን ፎቶዎች ማየት እችል ይሆን በማለት በትህትና ጠየቀችኝ።

የልጅቱን ጥያቄ ያለምንም ማንገራገር ተቀበልኩና ፎቶዎችን እያየው ወደስዋ አስተላልፈው ጀመር። ልጅቱ ሁሉንም ፎቶዎች አገለባብጣ ካየች በውሀላ ፎቶው ጋ በተደጋጋሚ አብሬያቼው ስለተነሰዋቼው ልጆች መጠየቅና ስለነሱ ማወቅ እንደምትፈልግ በፈገግታ ነገረችኝ።

እኔም የጓደኞቼን ፎቶ ተቀብየ በስነ ስርአት ለማስረዳትና ስለ ጓደኞቼ ታሪክ ለመናገር ና ለማስረዳት ያክል በትውስታ መስመር ከባህር ዳር ወደ አዲስ አበባ ከሚወስደን መኪና በሀሳብ ሰመመን ተመልሼ ባህር ዳር ገብቼ ስለነበርን የጓደኝነት ሁኔታ ማሰብና ማስታወስ ጀመርኩ። ትረካየንም በተረጋጋ መንፈስ የንዱን ጓደኛየን ፎቶ እየነካው መናገር ጀመርኩ።

ይሄ ጓደኛየ ብርሀኑ ይባላል እድሜው 17 ይሆነዋል። የ10ኛ ክፍል ተማሪ ነው። ይሄ ልጅ ሴት በጣም ነው እሚወደው። ግን ማናገር ስለሚፈራ ወድዋት ነው እሚቀረው እንጅ እስዋ ካልፈለገች እሱ አያናግራትም። ይሄኛው ደግሞ ዳንኤል ይባላል። 

10ኛ ክፍል ካጠናቀቀ 2አመት ሆኖታል። ሴት ናት የተባለች አታመልጠውም። መልክ ሀብት ምናምን አይልም ብቻ ግን ተቀምጣ ትሸናለች ከተባለ ለሱ ምርጫው ነች። ግን ሴቶች ሁሉ እንደሱ ስለሚመስሉት በጣም ነው የሚጠላቸውና የሚጠነቀቃቼው። ያለ ኮንዶም በፍፁም ሴክስ አያደርግቼውም።  

ይሄ ደግሞ መልካሙ ይባላል። የዩንቨርስቲ ተማሪ ነው በቀጣይ አመት ይመረቃል። መልካሙ በትምህርቱ በጣም ጎበዝ ነው። ግን አንዴ ወደየልጅነት 11ኛ ክፍል እንዳለፈ አቋርጦት ነበር። ምክንያቱም ፍቅር ነው። በጣም የሚያፈቅራትና የምታፈቅረው የነበረች ፍቅሩ አሜሪካ ልውሰድሽ ብሎ አታሎ በተዋት ሰውየ የከዳችውን ማስቴን ለመርሳት በሚል ምክምያት ነበር ያቋረጠው። 

መልኬ በትምህርቱየያዘው በጣም ጎበዝ ሰለነበር ቤተሰቦቹና አንዳንድ መካሪወቹ ጉትጎታ ማስቴን እረስቶ ወደ ትምህርቱ ተመልሶ አሁን ሊመረቅ አመትና ቀጣይ 1አመት ብቻ ነው የቀረው ግን መልኬ ከዛህን ጊዜ ወዲህ ሴት የተባለች እርሜ ብሎ ተቀመጠ።  

ሴት የተባለች ባጠገቡ ባታልፍ ደስታው ነው። አይደለም የሰውና የእንስሳም ቢሆን አትለፉብኝ የሚል ነው እሚመስለኝ።
ኦ !! ይቅርታ ስለኔ ሳልነግርሽ እኔ ያው እንደምታይኝ ለማያቁኝና ለሚጠሉኝ ነው እንጅ የማላምረው ለእናቴ ወርቅ ነኝ። እየቀለድኩ እንዳይመስለሽ ከምሬ ነው። ከወርቅም የበለጠ ወርቅ እንደሆንኩ ደጋግማ ስለምትነግረኝ ነው። 

እናትዬ እወድሻለሁ ግን ግን የማልዋሽሽ ነገር ቢኖር የመልኬ የድሮ ፍቅረኛው ጋ ተልኬ ስሄድ ምን ትለኝ ነበር መሰለሽ "አንተ የሆንክ አስፓልት ፊት" ምን አርጊ ነው እምትሉኝ። ስትለኝ እኔም ተልኬ ነው ብየ ንግግሬን ልጀምር ስጣደፍ ትቀጥልና 

ያንን መናጢ ደሀ ጓደኛህን ስትለው ድሀ ሲሰራና ሲማር እንጅ ሲያፈቅር አያምርበትም በለው ትልና አንተ ደግሞ እሱን ቅ/ሚካኤል የደበደበውን የሚመስለውን ፊትህን በዚህች መኪና ሳልገጭልህ እያለች መኪና እንደተገዛላት በጠቋሚ እጣትዋ ስታሳየኝ በንግግሯ ተናድጄ ወደ መጣውበት እበራለሁ።

አሁንም ይቅርታ ልጠይቅሽ ይቅርታ ፣አሽና አመሰግናለሁ እሚባሉት ቃላቶች ለሰው ልጅ አስፈላጊ ስለሆኑ ልንጠቀማቼው ይገባል። ስሜ ♥ናትናኤል ይባላል። እኔ ከጓደኞቼ አስበልጨ የምደወው እዮብን ነው። 

ምክናቱም ዳንኤል ሴትን ልጅ በመበቀል ስራ ተጠምዶ እንዲያቆም ስንጠይቀው መልካሙን ያሳመመችው ሴት ልጅ መልሳ አክማ እስክታድነው ድረስ ሴትን አልምርም እያለ ሴቶችን በማጭበርበር ና በመቅረብ ከሚያገኛት ሴት ጋ ሴክስ ያደርጋል። እኔም ይህንን ተግባሩን አልወድለትም። 

መልካሙ ደግሞ እፆታዋ ሴት የሆነች ሁሉ ተጎድታ ፣ታማ፣እቦዋት፣ወድቃ ተሰብራ፤ ወይም ወንድም ቢሆን እባክህንችእርዳኝ ብሎት ሚስቴ ልትሞትብኝ ነው ወይ እህቴ ወይ ፍቅረኛየ ካለው እንደቆመ ብትሞት ነው እሚመርጠው እንጅ አይረዳውም። ለሱ ሁሉም ሴቶች አንድ ናቼው። 

ብርሀኑም አንድ ችግር አለበት። የሴቶችን የማይቀርበው የተከዳውን መልኬን በማየትና በሚያተራምሰው ዳንኤልን ሲያይ ከዳኒ ጋ የሚተኙት ሴቶች ሁሉ እንደ ዳኒኤል ናቼው ብሎ ስለሚያስብ ነው። እናም እዮብም ከነሱ እማስበልጥበት ምክንያት ይሄው ነው። 

እዮባ አንድ ምርጥ አባባል አለችው። መልካም ሴት በትዕግስት እንጅ በፍለጋ አትገኝም ብሎ ስለሚያምን ነው። እኔ ግን አንደሱም አይደለሁም። እስከ 8 አመቴ ድረስ ገጠር ሲሆን ያደኩት ከዛ በ1988 ጥር17 ባህር ዳር ከተማ ገባን።

በዚህ ወቅት የኤች አይቪ በሽታ እየተስፋፋና እየተነገረለት የነበረበት ወቅት ሰለነበር አባቴ ሴት የምትባል ንገር ቀትቤ ካወራሁና አብሬያት ከተቀመጥኩ ኤች አይቪ ይዞኝ እንደምሞትና ከቤትም እንደሚያባርረኝ በሰፊው ይሰብከኝ ሰለነበር ቃሉን ስላጓድል እስከ 7ኛ ክፍል ድረስ በፍቅርና በደስታ ቤተሰቤ ጋ እያሳለፍኩ ባለውበት ላይ 7ኛ ክፍል እንደገባው አንድ አዲስ ነገር ተከሰተ.. ........

ክፍል 2 ይቀጥላል

ከወልቃይት ጠገዴ የተፈናቀሉ ወጣቶች በአዲስ አበባ - [ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው]

ከወልቃይት ጠገዴ የተፈናቀሉ ወጣቶች በአዲስ አበባ

ከወልቃይት ጠገዴ የተፈናቀሉ ወጣቶች በዚህ መልክ አብን ቢሮ ይገኛሉ። ወጣቶቹ ወደ አዲስ አበባ ሲመጡ ፍትህ እናገኛለን ብለው ነበር።  


ሆኖም የፌደራልና የአዲስ አበባ ፖሊስ የአብንን ቢሮ ከብቦ ወጥተው አቤቱታቸውን እንዳያሰሙ አግዷቸዋል። "ከወጡ እንተኩሳለን" እያለ መዛቱ ተገልፆአል።

ለወጣቶቹ ተራ ጀሮ ጠቢና ፖሊስ መላኩ አይደለም የሚገርመው። አንድ ከሰራዊቱ የወጣና በየጋዜጣው "ሪፎርም ያስፈልጋል" ሲል የምናውቀው ጀኔራልም ሁኔታውን ለማየት በቢሮው በኩል ሲያልፍ ተመልከቻለሁ። እንግዲህ የትህነግን ሰላዮች ስምሪት የሚቆጣጠረውና ወደ መቀሌ ሪፖርት የሚያጠናቅረው ይህ ጀኔራል ይሆናል።
ከወልቃይት ጠገዴ የተፈናቀሉ ወጣቶች በአዲስ አበባ
ወልቃይት ጠገዴ 1983 ዓ.ም በትግራይ መንግስት በኃይል መያዙ ይታወሳል፡፡ የትግራይ መንግስት ወልቃይት ጠገዴ የማንንት ጥያቄ ባቀረቡ የወልቃይት አማራዎች ላይ አስር፤ሰቆቃ፣ ግድያ ሲፈፀም ቆይቷል፡፡

የትግራይ መንግስት አማራዎችን በማፈናቀል በአንፃሩ የህዝቡን ስብጠር ለመቀየር ትግሬዎችን ከአድዋ፣ ከአድግራት፣ ከአንደርታ፣ ከአክሱም… ወዘተ በማምጣት በወልቃይት ለም መሬቶች ላይ አስፍሯል፡፡

በአካባቢው የትግራይ መንግስት በዘረጋው የአፈና መዋቅር የወልቃይት ጠገዴ አማራ ተወላጅ ላይ የተጠና አስተዳደራዊ በደል እየፈፀመ ይገኛል፡፡ ከወልቃይት ጠገዴ የተፈናቀሉ ወጣቶች በአዲስ አበባ
የኢፌድሪ ጠቅላይ ሚኒስቴርም እየተፈፀመ ያለውን በደል እንዲረዳና አስቸኳይ መፍትሔ እንዲሰጠን የሚከተሉትን ዋና ዋና ጥያቀዎቻችን እናቀርባለን፡፡

  • የትግራይ መንግስት በወልቃይት ጠገዴ አማራ ላይ የሚፈፅመውን ግድያ፣ አፈና፣ሰቆቃ፣አስር እና መፈናቀል በአስቸኳይ እንዲያቆም 
  • የወልቃይት ጠገዴ አማራዋች በቋንቋችን በአማርኛ የመናገር የመማር የመፃፍ፤በበህላችን ሀዘንና ደስታችን የመግለፅ መብታችን አንዲከበር
  • በትግራይ መንግስት የሚፈፀም የመሬት ዝርፊያ እንዲቆምልን እና ሐብት ንብረት የማፍራት መብታችን እንዲረጋገጥ
  • በማንነታቸው ምክንያት ከወልቃይት ጠገዴ ተፈናቅለው ሶሮቃ ጎንደር አዲስ አበባ በጊዚያዊ መጠለያ የሚገኝ የወልቃይት ጠገዴ አማራዎች በአስቸኳይ ወደ ትውልድ ቀያቸው እንዲመለሱና የተረጋጋ ሕይወት እንዲመሩ እንዲደረግ

  • ትግራይ ፀጥታ አካላት ወልቃይት ጠገዴን ለቀው እንዲወጡ እና የፌደርል የፀጥታ አካላት በቦታው እንዲተኩ እንዲደረግ
  • የወልቃይት ጠገዴ አማራ ማነንነት ጥያቄ በአስቸኳይ እንዲመለስ 
  • ወደ ወልቃይት ጠገዴ የመጡ የትግራይ ሰፋሪዎች በማንነታችን ጥያቄ ላይ የሚፈፅሙትን ሴራና ደባ እንዲቆሙልን
ለወጣቶቹ ድጋፍ ማድረግ የምትፈልጉ አራት ኪሎ ግንፍሌ ከድልድዩ ወደ ጃንሜዳ በሚወስደው መንገድ በኩል የሚገኘው የአብን ቢሮ በመሄድ ማገዝ ትችላላችሁ።
ከወልቃይት ጠገዴ የተፈናቀሉ ወጣቶች በአዲስ አበባ

ከወልቃይት ጠገዴ የተፈናቀሉ ወጣቶች በአዲስ አበባ

ከወልቃይት ጠገዴ የተፈናቀሉ ወጣቶች በአዲስ አበባ

የእውነተኛው የአፍሪካ አባት ሐውልት በጥር ወር ይጠናቀቃል! (አቻምየለህ ታምሩ)

የእውነተኛው የአፍሪካ አባት ሐውልት በጥር ወር ይጠናቀቃል! (አቻምየለህ ታምሩ)

በወያኔ የአፓርታይድ አገዛዝ ተቃውሞ ቢቀርብበትም በጋና መንግሥት ብርታትና ግፊት የሌሎችን የአፍሪካ አገሮች ይሁንታ በማግኘቱ በአፍሪካ ኅብረት ቅጥር ግቢ ግንባታው የተጀመረው የእውነተኛው አፍሪካ አባት የግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሐውልት በመጪው ጥር ወር እንደሚመረቅ ኅብረቱ አስታውቋል።

መለስ ዜናዊ ክዋሜ ንክሩማህን የአፍሪካ አባት ያደረገው ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን ያዋረደ መስሎት ነበር። ሆኖም ግን እውነት ይዘገያል እንጂ ተደብቆ አይቀርምና በእውነተኛ የአፍሪካ ልጆች ተጋድሎ የእውነተኛው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት አባት መታሰቢያ ሐውልት ለምርቃት ሊበቃ ነው። 


የሚጣላ ሕሊና ያላቸው ሰዎች እስካሉ ድረስ ለእውነት የደከሙ ደዎች ስም፣ ታሪክና ስራ አንድ ቀን ከመቃብር በላይ መዋሉ አይቀርም!

ከታት የታተመው ድምጽ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የመጀመሪያው የክብር ፕሬዝደንት የሆኑት ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እንዲመሰረት ግንቦት 14 ቀን 1955 ዓ.ም. ያሰሙት ታሪካዊ ንግግር ነው።

በግርማዊ ጃንሆይና ረዳቶቻቸው የረቀቀ ዲፕሎማሲ ጥረት ወደ አዲስ አበባ ለጉባዔ የተጋበዙት ነፃ የወጡ የአፍሪካ መሪዎች ኢትዮጵያ ያዘጋጀችውን የኅብረቱን ቻርተር የፈረሙት በዚህ የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ታሪካዊ ንግግር በቀረበላቸው ጥሪ መሰረት ነበር።

መረጃ በአሰቦት ገዳም ጉዳይ - ሃብታሙ አያሌው



መረጃ በአሰቦት ገዳም ጉዳይ - ሃብታሙ አያሌው

ከአንድ ሳምንት በፊት አመሻሽ ላይ ወደ ገዳሙ የመጡት ማንነታቸው ያልታወቁ የታጠቁ ኃይሎች መነኮሳቱ ገዳሙን ለቀው እንዲሄዱ በማስፈራራታቸው ደውል ተደውሎ ምዕመናን ሲሰባሰቡ ታጣቂዎቹ ሸሽተው ወደ ጫካው መግባታቸው እና በቀጣዩም ቀን ወደ መነኮሳቱ መኖሪያ ድንጋይ ሲወረወር ማምሸቱም ተነገረ።

የገዳሙ መነኮሳት ለወረዳው ፖሊስ ጣቢያ ስጋታቸውን በፅሑፍ አስገቡ። ያንን ተከትሎ ወረዳው የመደባቸው ታጣቂ ሚኒሻዎች በቦታው ሲደርሱ ከገዳሙ ጠባቂዎች ጋለ አለመግባባት ተከሰተ። 


የወረዳው ፖሊስ ከአንድ ጋዜጠኛ ለቀረበለት ጥያቄ ሲመልስ መነኮሳቱ ስጋታቸውን እና የተፈጠረውን ሁኔታው በፅሑፍ ማቅረባቸውን አምኖ፤ ፖሊስ ድጋፍ ለመስጠት ከላካቸው ሚኒሻዎች ጋር የተፈጠረው አለመግባባት ግን ባለመተዋወቅ የተከሰተ እንደሆነ መፍትሄ እንደተሰጠው ተናግሯል። 

አያይዞም አሁን የገዳሙ ጠባቂዎች እና በወረዳው የተመደቡ ሚሊሻዎች በጋራ እየጠበቁ ነው ሲል ምላሽ ሰጥቷል።

ለአንድ ሳምንት የዘለቀው አስጨናቂ የገዳሙ ሁኔታ በቤተክርስቲያን ጉዳይ ታዋቂ የሆነው "ሐራ ተዋህዶ" ዌብሳይትን ጨምሮ በርካታ ሚዲያዎች ሲዘግቡት ቆይተዋል። 

በተለይም ገዳሙ የሚገኘው የተደራጁ ኃይሎች የሐረርን ህዝብ በውሃ ጥም እየቀጡ እንዲሁም በጥቅሉ ከድሬዳዋ እስከ ሐረር መኪና እያስቆሙ እየዘረፉ ባለበት አካባቢ መሆኑ። ይህ ሁኔታም በመንግስት ሚዲያዎች እና በአካባቢው ጉዳተኞች እየተነገረ በመሆኑ ሁኔታው በእጅጉ ብዙዎችን አስጨንቋል።

ባለሁበት አገር ለሊቱ በመንጋት ላይ እስከሚገኝበት ሰዓት የገዳሙን ሁኔታ በመከታተል ያገኘሁት መረጃ ከላይ የተመለከተውን ነው። አንድ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የገዳሙ ነዋሪ የሚዲያውን ተፅዕኖ ተከትሎ መነኮሳቱ ምንም አልተፈጠረም እንዲሉ እና ስጋቱን አሳንሰው እንዲናገሩ እንደታዘዙ ሚዲያም ለዚሁ ጉዳይ ወደ ቦታው እንደሚላክ ጠቁመዋል።

ዋናው እና ተፈላጊው ነገር የፖለቲካ እሰጥ አገባው ሳይሆን የታሪክ አሻራ የሆነው ገዳም እና መነኮሳቱ ደህና መሆናቸው ነው። በቅርቡ በሶማሌ ክልል በርካታ አብያተ ክርስቲያናት የወደሙት እና መነኮሳት በቁም በእሳት አርረው እንዲከስሉ የተደረጉት ከሶስት ወራት በፊት የደረሰባቸውን ዛቻ ሲናገሩ ሰሚ በማጣታቸው እንደሆነ የተገለፀው ከጉዳቱ መድረስ በኋላ ነው።

የወረዳው ፖሊስ ሚሊሻ መመደቡን መግለፁ የሚያስመሰግን ነው። የክልሉ መንግስት ግን በየቦታው ሚሊሻ መድቦ እሳት በነደደበት ሁሉ እሩጦ መፍትሄ ለመስጠት መሞከር ብዙ እርቀት አይወስደውምና አሁንም በህግ የበላይነት መከበር በኩል የዜጎች ደህንነት በአስተማማኝ ሁኔታ እንዲጠበቅ ሊያደርግ ይገባል።

ችግር እያድበሰበሱ እያቃለሉ እየሸፋፈኑ ማለፍ አይበጅምን የፖለቲካ ድራማው ቀርቶ እውነተኛ መፍትሄ ይሰጥ። ነገሩን መካድ ችግሩን አይፈታውም። 27 ዓመታት በዚህ መንገድ ኑረናል። እናትን በጥይት የደፉት ልጇን ታሞ ነው የሞተው ሲያሰኙ ሰምተናል።  

ደህንነት ቢሮ ሲደበድቡት የሞተው የሐረሩን ኑረዲንን አስከሬኑን በገመድ አንጠልጥለው ተፀፅቶ ሞተ ብለው በኢቲቪ አሳይተው ደም አስነብተውናል። እውነት የወጣው ዘግይቶ ነው እናም የአሰቦት ገዳምን ጉዳይ እንደ እንደዛ ለማድረግ ባትሞክሩ ጥሩ ይመስለኛል።
ቢያንስ ገዳሙ በጋራ እየተጠበቀ መሆኑ እፎይታ ነው። ምንም ያልተፈጠረ ለማስመሰል መሞከረ መተማመንን
የባሰ ገደል ይከታልና ተወት አድርጉት።


"ማንነትን የመለሰ ፌዴራሊዝም ስህተቱን የሚያርምበት አቀበት ላይ መላ ሊያጣ አይገባም" - ጥናት



"ማንነትን የመለሰ ፌዴራሊዝም ስህተቱን የሚያርምበት አቀበት ላይ መላ ሊያጣ አይገባም" - ጥናት

  • ‹‹ሕገ መንግሥቱ የወልቃይት እና የራያን ጥያቄ መመለስ ያልቻለው ሕዝቦቹ በየት እንደሚተዳደሩ ቅድሚያ ስላልተጠየቁ ነው፡፡››
  • ‹‹ኢትዮጵያ ውስጥ ሕገ-መንግሥት ተጻፈ እንጂ አልተተገበረም፡፡›› የፖለቲካ ሳይንስ ምሁር
  • ‹‹አሁን የወልቃይት ጥያቄ የማንነት እና የመሬት ይገባኛል ብቻ ሳይሆን ዴሞክራሲ እና ችግሩን የሚፈታ ሕገ መንግሥት ጭምር ነው›› ዶክተር ሶኛ ጆን
  • ‹‹ማንነትን የመለሰ ፌዴራሊዝም ስህተቱን የሚያርምበት አቀበት ላይ መላ ሊያጣ አይገባም፡፡›› ጥናት
ባሕር ዳር፡ጥቅምት 16/2011 ዓ.ም(አብመድ) የባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ሳይንስ እና ዓለም አቀፍ ጥናት ትምህርት ክፍል መምህሩ ቻላቸው ታረቀኝ ‹‹ሕገ መንግሥቱ የወልቃይት እና የራያን ጥያቄ መመለስ ያልቻለው ሕዝቦቹ በየት እንደሚተዳደሩ ቅድሚያ ስላልተጠየቁ ነው፡፡ አንቀፅ 46 የግዛት ወሰን ላይ ቋንቋ፣ አሰፋፈር እና የሰዎች ይሁንታ ይላል፡፡

ነገር ግን በ1984 ክልሎች ‹አንድ፣ ሁለት …› ተብለው ሲለዩ የተካለሉበት በ1987 ሕገ-መንግሥቱ ሲፀድቅ ያለ ሕዝብ ይሁንታ በዚያው ቀጥሏል›› ብለዋል፡፡ ይህም አሁን ላሉት ሕገ-መንግሥታዊ ጥያቄዎች በር መክፈቱንም ጠቁመዋል፡፡


መምህር ቻላቸው ‹‹የሕዝቦች ፍላጎት ቀሰበቀስ ሲቀሰቀስ በዛ ልክ የተሰፈረው ሕገ-መንግሥት መመለስ የሚችልበት አቋም ላይ አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ሕገ-መንግሥት ተጻፈ እንጂ አልተተገበረም፤ የፖለቲካ ወገንተኝነት እና ጥገኛ ተቋማት እንደአሸን ነበሩ፡፡  

አሁንም ችግሩን ለመፍታት በሕገ-መንግሥቱ ታሪካዊ ማንነት ሊካተት ይገባል›› በማለት መፍትሔ ያሉትን ሐሳብም ምሁሩ ሰንዝረዋል፡፡ የግዛት ወሰን ችግሮች ሲኖሩም መፍትሔውን ጥያቄ ለሚነሳበት ክልል መንግሥት ከመስጠት ይልቅ የፌዴራል መንግሥት የሚወስንበት አሠራር ቢኖር እንደሚሻልም ተናግረዋል፡፡

የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ፖለቲካል ሳይንስ እና የዓለምዓቀፍ ጥናት ትምህርት ክፍል ተመራማሪው ዶክተር ሶኛ ጆን ደግሞ ‹‹የኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት እና የወልቃይት ጥያቄ ሆድና ጀርባ ናቸው›› የሚል ሐሳብ አንስተዋል፡፡ ‹‹የዜጎች ጥያቄ እና የሕገ መንግሥቱ ዝምታ ከጊዜ ወደጊዜ አሳሳቢ ነው፡፡  

የወልቃይት ነዋሪዎች አንቀፅ 39 ባለው መብት እና አንቀፅ 46 ባስቀመጠው መሠረት ‹ቋንቋችን፣ ማንነታችን እና ባሕላችን አማራ ሁኖ ሳለ በሌላ ክልል እንተዳደራለን› የሚል ቅሬታ አላቸው፡፡ ሕገ-መንግሥቱ በቀጥታ እኛን ያላማከለ ውሳኔ በማሳለፉ ለሰብዓዊ መብት ጥሰት እና እስር እየተዳረግን ነው›› ማለታቸውን ጥናታቸውን ዋቢ አድርገው ዶክተር ጆን ገልጸዋል፡፡ 

‹‹አሁን የወልቃይት ጥያቄ ‹የማንነት እና የመሬት ይገባኛል› ብቻ ሳይሆን ዴሞክራሲ እና ችግሩን የሚፈታ ሕገ-መንግሥት ጭምር ነው›› ብለዋል ዶክተር ሶኛ ጆን፡፡ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመጡት ጥናት አቅራቢ መምህር ቢንያም መኮንን ደግሞ ‹‹በብሔር ላይ የተመሠረተው ፌዴራሊዝም የሕዝቡን ምጣኔ ሀብታዊ ፍላጎት የመመለስ ፈተና ላይ ወድቋል፡፡  

ማንነትን የመለሰ ፌዴራሊዝም ስህተቱን የሚያርምበት አቀበት ላይ መላ ሊያጣ አይገባም፡፡ የግለሰብ ነፃነት ላይ የተመሠረተ፣ ምጣኔ ሀብታዊ ተጠቃሚነትን ሊያሻሽል የሚችል ሥርዓት መፍጠር መፍትሔ ነው፡፡ ከማንነት ባሻገር ደግሞ የጋራ እሴቶችና ጥቅሞች ላይ መረባረብ ያስፈልጋል›› ብለዋል፡፡

ሦስተኛው ዓለም አቀፍ የፖለቲካ ሳይንስ ምሁራን የጥናትና ምርምር ዓውደ ጥናት በባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ ዘጠኝ ምርምሮች ቀርበውበት ተጠናቋል፡፡

ዘጋቢ፡-ግርማ ተጫነ


የጋምቤላ ክልል ፕሬዝዳንት ስልጣን ለቀቁ



የጋምቤላ ክልል ፕሬዝዳንት ስልጣን ለቀቁ

(ኢሳት ዲሲ–ጥቅምት 16/2011) የጋምቤላ ክልል ፕሬዝዳንት ስልጣናቸውን ለቀቁ። አዲስ ፕሬዝዳንትም ተሰይሟል።

በአዲስ አበባ ለአንድ ሳምንት ግምገማ ሲያደርግ የቆየው የጋምቤላ ክልል ገዢ ፓርቲ በገዛ ፈቃዳቸው የለቀቁትን ሊቀመንበሩንና ምክትላቸውን በሌሎች መተካቱን የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

የጋምቤላ ህዝቦች አንድነት ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ ሊቀመንበርና የጋምቤላ ክልል ፕሬዝዳንት አቶ ጋትሉዋክ ቱትና ምክትላቸው አቶ ሰናይ አኩዎር ይቅርታ ጠይቀው በለቀቁበት የአዲስ አበባው ግምገማ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ መገኘታቸውን ለማወቅ ተችሏል።

በጋምቤላ የጋትሉዋክ ቱት አመራር ከስልጣን እንዲወርድ የተቃውሞ ሰልፍ ሲደረግ ቆይቷል። በዚህ ተቃውሞ በተወሰደ የሃይል ርምጃም በትንሹ አስር ሰዎች መገደላቸው ይታወሳል። ለወራት የዘለቀው የህዝብ ጩሀት በመጨረሻም ሰሚ አገኘ።

የጋምቤላ ክልል ነዋሪ አመራሩ እንዲነሳለት ህይወቱን የገበረለትን ተቃውሞ ሲያደርግ ነበር የቆየው። ባለፉት ሶስት ወራት በሀገር ውስጥና በውጭ የሚኖሩ የክልሉ ተወላጆች ለፌደራሉ መንግስት ጥያቄ ሲያቀርቡ እንደነበር ይታወሳል።

በአመራር ላይ ያለው የጋትሉዋክ አስተዳደር በኢትዮጵያ የመጠውን የለውጥ ሂደት የሚያደናቅፍ ከመሆኑ ባሻገር የህወሀት የጭቆና አገዛዝን ማስቀጠል የመረጠ በመሆኑ በአስቸኳይ ይነሳ የሚለው ጥያቄ ተነስቷል።

ተቃውሞው በተለይ የክልሉ ፕሬዝዳንት ላይ ያነጣጠረ ነበር።

ለዚህም ሁለት ምክንያቶች ይነሳሉ። አንደኛው የክልሉ ፕሬዝዳንት ጋትሉዋክ ቱት በትውልድ ደቡብ ሱዳናዊ በመሆናቸው በስደት ወደኢትዮጵያ ለገቡትና በቁጥር በጋምቤላ ነዋሪ የሆኑ ኢትዮጵያውያንን ለሚበልጡ ደቡብ ሱዳናውያን ያደላሉ የሚል ነው።

ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ ከህወሀት አገዛዝ ጋር እጅና ጓንት ሆነው የክልሉን ህዝብ ለጭቆናና ብዝበዛ እየዳረጉት እንደሆነ ይጠቀሳል።

የህወሃት ዘመን አፈናና በደል ጋምቤላ ተጠናክሮ መቀጠሉን ህዝቡ በምሬት ይገልጻል።

በቅርቡ ለውጡን ለመታዘብ ሀገር ቤት የገቡትን በትውልድ ኢትዮጵያዊ በዜግነት አሜሪካዊ የሆኑት ዶክተር ማኛንግን ጨምሮ ከ10 በላይ አክቲቪስቶችን የግትሉዋክ ቱት አስተዳደር ማሰሩ ተቃውሞውን አጠናክሮታል።

የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ ፕሬዝዳንት አቶ ኦባንግ ሜቶ ወደ ጋምቤላ ባመሩ ጊዜ የጋቱዋክ ቱት አመራር የፈጠረውን ችግር መነሻ በማድረግ በአዲስ አበባ መግለጫ የሰጡት አቶ ኦባንግ የፌደራሉ መንግስት በጋምቤላ አስተዳደር ላይ እርምጃ እንዲወስድ መጠየቃቸውም የሚታወስ ነው።

ለወራት የህዝብ ብሶትና እሮሮ ከተሰማ በኋላ ትላንት ምላሽ መገኘቱን ነው የደረሰን መረጃ የሚያመለክተው።

አዲስ አበባ የገቡትና ግምገማቸውን ከጀመሩ አንድ ሳምንት የሆናቸው የጋምቤላ ህዝቦች አንድነት ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ ጋህአዴን የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ከአንድ ውሳኔ ላይ መድረሳቸውን አሳውቀዋል።

ህዝብ ለውጥ እንደሚፈልግ፣ አመራሩ እንቅፋት ሆኖ እንደቆየ አባላቱ ጠንከር ያለ ግምገማ ማድረጋቸውን ተከትሎ የህዝብ ተቃውሞ የቀረበባቸው አቶ ጋትሉዋክ ቱትና ምክትላቸው አቶ ሰናይ አኩዎር በገዛ ፈቃዳቸው ስልጣናቸውን መልቀቃቸው ተስምቷል።

ፓርቲው አቶ ኦሙድ ኡጁሉን የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ አኙአያ ጃከን ደግሞ ምክትል ሊቀመንበር አድርጎ መምረጡም ታውቋል፡፡ አቶ ኦሙድ የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሆነው ክልሉን እንደሚመሩ ነው የተገለጸው።

በግምገማው ላይ ጠቅላይ ሚንስትር ዶክተር አብይ አህመድ መገኘታቸው ታውቋል።

የክልሉ ህዝብ ልማት የተጠማ በመሆኑ አዲሱ አመራር ጊዜውን በግል አጀንዳዎችና ሽኩቻ ከማጥፋ ይልቅ ራሱን ከጎሰኝነትና ከጥላቻ በማጽዳት የክልሉን አመራር በማጠናከር የህዝቡን ችግር ሊፈታ እንደሚገባ ማስገንዘባቸውን የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አቶ ፍጹም አረጋ ገልጸዋል።

ከኃላፊነት የተነሱት አመራሮችም በድርጊታቸው ተጸጽተው ይቅርታ መጠየቃቸው እና ህዝቡን ለመካስ በተመደቡበት የስራ መስክ ለመሰማራት መወሰናቸውም ተመክልቷል።

ኢሳት ያነጋገራቸው የጋምቤላ አክቲቪስቶች ግን የጋትሉዋክ አመራር አባላት ለፈጸሙት የግድያና የዘረፋ ወንጀል በህግ ሊጠይቁ ይገባል ባይ ናቸው።


የአክቲቪስቱ የፍቅር ደብዳቤ (አሳዬ ደርቤ)



የአክቲቪስቱ የፍቅር ደብዳቤ (አሳዬ ደርቤ)

ለምወድሽ……. እንዴት ነሽ? እኔ አንቺን ካፈቀርኩበትና አክቲቪስት ከሆንኩበት ጊዜ አንስቶ ደህና ሆኜ አላውቅም፡፡

በአገሬ ፍቅር ላይ ያንቺ ፍቅር ተጨምሮ እያቅበዘበዘኝ ነው፡፡ አሁን አሁንማ… ምግብ መብላትም ሆነ መንግስትን መተቸት አቅቶኛል፡፡ የማገኘው የላይክ ቁጥርም በእጅጉ ቀንሷል፡፡ 


የኔ ውድ፡- ለባለፉት ዓመታት የፖሊስ ኮሚሽነር እንጂ ፍቅር ይይዘኛል ብዬ አላስብም ነበር፡፡ ከአገሬ ተርፎ ለሴት የሚበቃ ፍቅር ይኖረኛል የሚል ግምትም አልነበረኝም፡፡ የሆነው ግን እንደዚያ ነበር!!

ባልታሰበ ቀን ከዐይኔ ገብተሽ እንቢተኛውን ልቤን እንደ ሜቴክ ዘረፍሽው፡፡ በመላ አካላቴ ላይ በመሰራጬት እንደ ህውኃት የመሬት ወረራ አካሄድሽብኝ፡፡ በፍቅርሽ ቦርቡረሽ በመግባት ጭንቅላቴ ውስጥ ኮማንድ-ፖስት አዋቀርሽብኝ፡፡ በማንነቴ ላይ ጥቃት ፈጸምሽብኝ፡፡ ከአብዲ ኢሌ በባሰ ወህኒ-ቤት ውስጥ አስገባሽኝ፡፡

የኔ አብዮት፡- ከወራት በፊት መንገድ ላይ አየሁሽ፡፡ እናም በአክቲቪስትነቴ በምታወቅበት አካውንቴ ላይ… ‹‹ይች አገር ወዴ'ት እየሄደች ነው?›› በማለት ፈንታ ‹‹ይች ልጅ ወዴ'ት እየሄደች ነው?›› የሚል ጥያቄ በመለጠፍ… ከኋላ ከኋላ እከተልሽ ጀመር፡፡ ያላንቺ እውቅና ዘይኑ ጀማልን በመሆን መዳረሻሽን መጣራቴን ተያያዝኩት፡፡ 

ሆኖም ግን በመጨረሻ ያየሁት ነገር እንደ ዶክተር አቢይ ስልጣን ‹‹ምነው በቀረብኝ›› የሚያስብል ነበር፡፡ ታከለ ኡማን ይመስል ቦሌ ላይ ከአንድ የባሌ ወጣት ጋር አፍ-ላፍ ገጥመሽ ስታወሪ እጅ-ከፍንጅ ያዝኩሽ፡፡ መቼስ በጊዜው እንዴት እንደተናደድኩ አትጠይቂኝ፡፡  

ከአቶ ታዬ ደንድኣ በላይ በጣም ስሜታዊ ሆኜ ነበር፡፡ ይሄም ሆኖ ግን …አፍቃሪሽ እንጂ ባልሽ ባለመሆኔ ‹‹እንዴት በኔ ላይ ይሄን ታደርጋለች?›› ብዬ ልወቅስሽ አልቻልኩም፡፡ ይልቅስ ሲጋብዝሽ ያየሁት ልጅ እንደ ኮሚሽነር ደግፌ በዲ አፍሶ ወደ ቤቱ ሳያስገባሽ በፊት ፈጠን ብዬ ከእጄ ላስገባሽ እንደሚገባ አመንኩኝ፡፡

እናም በአንዱ ምሽት በቻት ስጀነጅንሽ ከቆዬሁኝ በኋላ ‹‹ነገ አገኝሃለሁ›› የሚል ቀጠሮ ሰጠሽኝ፡፡ አዳሬንም አንጀትሽን የሚበሉ ቃላቶችን ሳሰባስብ አደርኩኝ፡፡ በማግስቱ ተገናኝተን ከፊትሽ ስቀመጥ ግን እንደ ዶክተር ደሳለኝና በቀለ ገርባ ልነግርሽ ያሰብኩት ሁሉ ጠፍቶኝ አረፈ፡፡  

ከዚያን ቀን በኋላም አንቺን ማግኘትና ኢትዮጵያን ማረጋጋት ህልም ሆኖ ቀረ፡፡ ምክንያቱም በድጋሜ ላገኝሽ ብዙ ጥረት ያደረኩ ቢሆንም… እንደ ፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ-ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ‹‹ቀጠሮ›› ከመስጠት ባለፈ በአካል አግኝቼሽ የልቤን ህመም እንዲነግርሽ አልፈቀድሽልኝም፡፡

የኔ ዉድ፡- አንቺን ካፈቀርኩበት ጊዜ አንስቶ ሃገራችን ላይ ስንት ክስተት እንደተፈራረቀ ታውቂያለሽ?
እኔ ከልብሽ ውስጥ መግባት አቅቶኝ ስፍገመገም ግንቦት ሰባትና ኦነግ ወደ ሃገር ቤት ገብተዋል፡፡ የኦሮማራ ጥምረት ተቀዛቅዟል። አዴፓና ህውኃት ጦር መማዘዝ ጀምረዋል፡፡ አንዱአለም ቡኬቶ የአንድ ፓርቲ ሊቀ-መንበር ሁኗል፡፡ ዘውዳለም ታደሰ ታፍሷል፡፡ (….ብቻ ምን አለፋሽ ብዙ ነገሮች ተከስተዋል፡፡)

እኔ ግን የፌስቡክ ተከታዮቼን ትቼ አሁንም ድረስ አንቺን እየተከተልኩ እገኛለሁ፡፡ መንታ መንገድ ላይ ያለች አገሬን ችላ ብዬ ጥላሽ በመሆን አብሬሽ እነጉድ ይዣለሁ፡፡ በፌክ አካውንቴ መንግስትን እንዳልርበደበድኩኝ በእውነተኛ ማንነቴ አንቺን ማሸነፍ አቅቶኝ እየተንገበገብኩ አገኛለሁ፡፡ የማፈቅራትን ሴት ማግኘት አብዮት ከማስነሳት በላይ ከባድ ሆኖብኝ እንደ ራያ ምድር እየታመስኩ እገኛለሁ፡፡ እንደ ሐረር ከተማ በጥም እቃትታለሁ፡፡
.
አንዳንድ ጊዜ ‹ከዚህ በላይ ላለመሰቃየት› እወስንና የለከፈኝን ፍቅር ዲአክቲቬት በማድረግ ወደ ቀድሞ አክቲቪስትነቴ ለመመለስ እሞክራለሁ፡፡ ሆኖም ግን ላፕቶፕ ከፍቼ መጻፍ ስጀምር መንግስትን በሚተች ርዕስ ስር አንቺን ሳወድስ እገኛለሁ፡፡ በዚህም የተነሳ የቀድሞ ማንነቴን መመለሱ ሕውኃትን ወደ ስልጣን ከመመለስ በላይ ከባድ ሆኖብኝ እገኛለሁ፡፡

የኔ ንግስት፡- የሆነ ጊዜ ወንድ አይተሸ የማታውቂ ‹‹ልጃ-ገረድ›› መሆንሽን አጫውተሽኛል፡፡ እናም ልታገኝኝ የማትፈልጊው በዚህ የተነሳ ከሆነ… እስክንጋባ ድረስ እንደ ኦነግ ሰራዊት ትጥቄን የመፍታት ፍላጎት ስለሌለኝ የሚያሳስብሽ ነገር አይኖርም፡፡ በህገ-መንግስቱ ላይ ያደበርኩትን ሰፊ ልምድ ክብረ-ንጽህናሽ ላይ በማዋል ልደረምስሽ የምፈልገው ከጋብቻ እለታችን በኋላ ነው፡፡

በማስከተል ደግሞ ስለ ኑሮ ደረጃዬ ልነግርሽ የምፈልገው ነገር ለሚስትነት ስመኝሽ የምትኖሪበት ቪላና የምትነጅው መኪና በጥሎሽ መልክ ላበረክትልሽ ባልችልም መሰረታዊ ፍላጎታችንን ሊሸፍን የሚችል ከአባይ ጸሐዬና ከበረከት ስምኦን የተሻለ ገንዘብ እንዳለኝ ግን ልነግርሽ እፈልጋለሁ፡፡ ከዚህ ባለፈ ደግሞ ላንች ያለኝ ፍቅር እንደ ስኳር ፋብሪካችንና እንደ አባይ ግድባችን የማያልቅ መሆኑን እንዲታውቂልኝ እሻለሁ፡፡  

ስለዚህም የአገራችን ህልውና ዶክተር አቢይ እጅ ላይ እንደወደቀው ሁሉ… የኔም ህልውና መዳፍሽ ውስጥ መግባቱን አውቀሽ የፍቅር ጥያቄዬን ትቀበይኝ ዘንድ እማጸንሻለሁ፡፡

በመጨረሻም… ‹‹አረሱት›› የሚለውን የፋሲል ደሞዝን ሙዚቃ በመጋበዝ በዚች የስንኝ ቋጠሮ እሰናበትሻለሁ፡፡

ወልቃይት የአማራ ራያ የወሎ
‹‹ይሁን›› ካለ ወዲያ በድንበር ከልሎ
አምላክ አንቺን ሰራ ‹‹የእሱ ሁኝ›› ብሎ፡፡ 


ኦብነግ መገንጠል እንደሚችል ከዐቢይ አገዛዝ ይሁንታ አግኝቷል! አቻምየለህ ታምሩ


ኦብነግ መገንጠል እንደሚችል ከዐቢይ አገዛዝ ይሁንታ አግኝቷል


የዐቢይ አሕመድ አገዛዝ ኦብነግ «ሶማሌ ክልል»ን ከኢትዮጵያ መገልጠል እንደሚችል አስመራ ላይ ስምምነት ላይ ደርሷል! የኢትዮጵያን የግዛት አንድነትና ዳር ድንበር የማይጠብቅ ስምምነት ከኦብነግ ጋር በማድረግ ኦብነግ ሶማሌ ክልልን መገንጠል እንደሚችል ስምምነት ላይ የደረሰው የዐቢይ አገዛዝ ትናንትና ካራማራ ላይ ኢትዮጵያውያን ሞተው መሬቱን ኢትዮጵዊ አድርገውታል ያለውን ምድር ነው። ድንቅም አገር ግንባታ!

ኦብነግ እ.ኤ.አ. በ2006 ዓ.ም. በሶማሊያ በወቅቱ ሞቃዲሾን ይዞ የነበረው የእስላማዊ ፍርድ ቤቶች ኅብረት የሽግግር መንግሥት አካል ነበር። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ውሳኔ (1724/2006) እንዳሳወቀው ሞቃዲሾን ይዞ ለነበረው ለእስላማዊ ፍርድ ቤቶች ኅብረት ጊዜያዊ መንግሥት ድጋፍ ይሰጡ ከነበሩ አገሮች መካከል ግብፅና ሳዑዲ ዓረቢያ ተጠቃሾች ነበሩ።

የሶማሊያ እስላማዊ ፍርድ ቤቶች ኅብረት አባል የነበረው ኦብነግ አላማው የዚያድ ባሬን ባለ አምስት ኮከብ ታላቋን ሶማሊያን መፍጠር ነው። በሌላ አነጋገር የዐቢይ አሕመድ አገዛዝ አስመራ ላይ ከኦብነግ ጋር የደረሰው ስምምነት በሳዑዲ ይደገፍ የነበረው የሶማሊያ እስላማዊ ፍርድ ቤቶች ኅብረት አባል የሆነው ኦብነግ የዚያድ ባሬን ህልም እንዲያሳካ ነው።

እንደሚታወቀው የኦብነግ ራዕይ ቀያሽ የሆነው ዚያድ ባሬ በኢትዮጵያ ላይ ጦርነት የከፈተው ባሌን፣ ሐረርጌንና አርሲን ጨምሮ እስከ ናዝሬት ድረስ ያለውን የኢትዮጵያ ግዛት የታላቋ ሶማሊያ አካል ናቸው የሚል ትርክት ፈጥሮ ነው። የዚህ ራዕይ ውሉድ የሆነው ኦብነግም አላማው ያው ተመሳሳይ ነው።

ጥያቄው ዐቢይ አሕመድ አስመራ ላይ ከኦብነግ ጋር ሶማሌ ክልል መገንጠል እንደሚችል የተስማማው ኦብነግ የሶማሊያ እስላማዊ ፍርድ ቤቶች ኅብረት አባል በነበረበት ወቅት ትረዳ የነበረችዋንና ለዐቢይ አገዛዝም ሶስት ቢሊዮን ዶላር የሰጡትን አረቦች ለማስደሰት ነው? ወይንስ የኢትዮጵያን የግዛት አንድነትና ዳር ድንበር ለማስጠበቅ? ለዚህስ ቀብድ ይሆን አረቦቹ ሶስት ቢሊዮን ዶላር ለዐቢይ አገዛዝ ሰጡ የተባለው?

የዐቢይና የኦብነግ የአስመራው ስምምነት የኦብነግ ደጋፊው ሻዕብያና የኦብነግ ደጋፊ የሆነችው ሳዑዲ ያስማማችው የሳዑዲው የኢሳያስና የዐቢይ አሕመድ ስምምነት አካል ይሆን?

የቢቢሲን ዘገባ እነሆ



በምሥራቅ ኢትዮጵያ የሶማሌ ክልል አማጺ ቡድን የሆነው የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃነት ግንባር እዚህ እንዴት ደረሰ?

የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃነት ግንባር (ኦብነግ) በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር ስምምነት ላይ መድረሱን የመንግሥት ከፍተኛ ባለስልጣናት እሁድ ዕለት ከአሥመራ አሳውቀዋል።

የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ወርቅነህ ገበየሁ እንደገለጹት የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃነት ግንባርና የኢትዮጵያ መንግስት በተለያዩ ጊዜያት ያደረጉትን ድርድር ተከትሎ ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ተናግረዋል።

በሌላ በኩል የግንባሩ የውጭ ግንኙነት ፀሐፊ አቶ አህመድ ያሲን ሼክ ኢብራሂም ከኢትዮጵያ መንግሥት ስለደረሱበት ስምምነት አስመልክቶ ለቢቢሲ ሶማልኛ እንደገለፁት፤ የሶማሌ ህዝብ ዕጣ ፈንታውን በነፃነት ራሳቸው መወሰን እንዳለባቸው ከስምምነት ላይ መደረሱን ነው።

ህዝቡ መብቱን በመጠቀም የራስን ዕድል በራስ ከመወሰን መብት በተጨማሪ ግንባሩም የሚታገልለትን አላማም በሰላም እንዲያስቀጥል ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ተናግረዋል።

በዚህም መሰረት የራስን ዕድል በራስ መብትን ለመወሰን ህዝበ- ውሳኔ እንዲካሄድና ህዝቡ ከኢትዮጵያ መገንጠል ከፈለገ ያ መብት እንዲከበር፤ መቆየትም ከፈለገ ያ ውሳኔ እንዲከበርለት ውሳኔ ላይ ደርሰናል ብለዋል።

ህዝበ ውሳኔውንም ለማስፈፀምም ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር የሁለትዮሽ ኮሚቴ እንደሚመሰረትም አስታውቀዋል።

ለበርካታ ዓመታት በምሥራቃዊው የሃገሪቱ አካባቢ የትጥቅ ትግል ሲያካሂድ የነበረው የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃነት ግንባር ወደ ሃገር ቤት ተመልሶ በሰላማዊ ትግል ውስጥ ለመሳተፍ መወሰኑ ለሃገሪቱ ሰላም በአጠቃላይ በተለይ ደግሞ ለሶማሌ ክልል ሰላም ጉልህ ሚና እንደሚኖረው ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

ኦብነግ ከኢትዮጵያ ለመገንጠል ትግል ያደርጉ ከነበሩ አማፂ ቡድኖች መካከል አንዱ ሲሆን እንደ አውሮጳውያን አቆጣጠር በ1984 ነበር የተመሰረተው። ቡድኑ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በኢትዮጵያ መንግሥት ሽብርተኛ ተብለው ከተሰየሙ ቡድኖች ዝርዝር ውስጥ ነበር።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ ሦስት የፖለቲካ ቡድኖች ከሽብር ቡድን ዝርዝር ውስጥ በፓርላማው ውሳኔ እንዲወጡ ከተደረገ በኋላ በውጪ የሚገኙ የታጠቁ ተቃዋሚዎች ወደ ሃገር ቤት መመለሳቸው ይታወቃል።

አማፂው አብነግ የኦጋዴን ሕዝብ ብሎ የሚጠራውን በምሥራቅ ኢትዮጵያ የሚገኘው የሶማሌ ሕዝብ የራስን እድል በራስ የመወሰን መብት ለማስከበር በፖለቲካዊና ወታደራዊ መስኮች ትግል ሲያደርግ ቆይቷል።

ኦብነግ ከምስረታው አስራ አራት ዓመታት በኋላ ከኢትዮጵያ ሶማሌ ዴሞክራሲያዊ ሊግ ጋር በመዋሃድ የሶማሊ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲን መስርተው ነበር።

ምን መቼ ሆነ?

ሚያዚያ 1996 ዓ.ም፡ የተቃዋሚ የሆነው ሬዲዮ ነፃነት ኦብነግ በኢትዮጵያ መንግሥት ኃይሎች ላይ በፈፀመው ጥቃት በርካታ ወታደሮችን መግደሉን ዘገበ።

መጋቢት 1998 ዓ.ም፡ የኦብነግ መሪዎች ከዴንማርክ መንግሥት ባለስልጣናት ጋር ተገናኝተው በኢትዮጵያ ያሉ ሶማሌዎች ላይ በመንግሥት ይፈፀማል ያሉትን የሰብዓዊ መብት ረገጣ አስረድተዋል። የዴንምርክ ባለስልጣናትም ያለው አስተዳደር ዴሞክራሲን የማይተገብር በመሆኑ ለኢትዮጵያ የሚሰጡትን እርዳታ አቋርጠዋል።

ጥር 2001 ዓ.ም፡ ኦብነግ ሼክ ሸሪፍ ሼክ አህመድ የሶማሊያ ፕሬዝዳንት ሆነው በመመረጣቸው የእንኳን ደስ አልዎ መልዕክት አስተላለፈ።

ጥቅምት 2002 ዓ.ም፡ የኦብነግ ኮምኒኬሽን ሃላፊ ሁሴን ኑር የፑንትላንድና ሶማሊላንድ አስተዳደሮች ከኢትዮጵያ ሸሽተው የሄዱ ሶማሌዎችን አሳልፈው ለኢትዯጵያ መንግሥት ይሰጣሉ ሲል ከሰሰ።

ነሐሴ 2002 ዓ.ም፡ ኦብነግ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር ስምምነት ላይ ለመድረስ ተቃርቧል የሚለውን ዘገባ አስተባበለ።

ጥር 2003 ዓ.ም፡ ከ400 የሚበልጡ የግንባሩ አመራሮችና አባላት ከእስር ተለቀቁ።

ሰኔ 2003 ዓ.ም፡ ኦብነግ ሽብርተኛ ቡድን ተብሎ በኢትዮጵያ መንግሥት ተፈረጀ።

ጥር 2004 ዓ.ም፡ ግንባሩ እንግሊዝ ውስጥ ባወጣው መግለጫ መንግሥት አጠቃላይ የሆነና በሦስተኛ ወገን አደራዳሪነት በገለልተኛ ስፍራ ላይ ለመደራደር ፈቃደኛ ከሆነ ኦብነግ ዝግጁ መሆኑን ገለፀ።

ጥቅምት 2005 ዓ.ም፡ ኦብነግ መስከረም ላይ በኬንያው የመከላከያ ሚኒስትር ሞሃመድ ዩሱፍ ሃጂ አደራዳሪነት ናይሮቢ ውስጥ ከመንግሥት ጋር ሲያደርገው የነበረው የሰላም ድርድር ተቋረጠ።

ጥር 2008 ዓ.ም፡ ኦብነግ በሶማሌ ክልል በሚካሄደው የነዳጅ ዘይት ፍለጋ የክልሉን ህዝብ ያላሳተፈ በመሆኑ የህዝቡን ጥቅም የሚያስከብር እርምጃ እንደሚወስድ በፍለጋው ላይ የተሰማሩን የውጪ ኩባንያዎችን አስጠነቀቀ።

ግንቦት 2009 ዓ.ም፡ ኦብነግ ከአርበኞች ግንቦት 7 ጋር በጋራ ለመስራት መስማማቱን ቡድኖቹ ባወጡት መግለጫ አሳወቁ። ሁለቱ ቡድኖች ጀርመን ፍራንክፈርት ውስጥ ለሦስት ቀናት ያካሄዱትን ስብሰባ ተከትሎ ነው ውሳኔያቸውን ያሳወቁት።

ነሐሴ 2009 ዓ.ም ፡ የሶማሊያ መንግሥት የኦብነግ ከፍተኛ አመራር የሆኑት አብዲካሪም ሼክ ሙሴን (ቀልቢ ደጋ) በሰሜን ሶማሊያዋ ከተማ አዳዶ ውስጥ ይዞ ለኢትዮጵያ መንግሥት መስጠቱን አረጋገጠ።

ሰኔ 2010 ዓ.ም ፡ የኢትዮጵያና የኤርትራ ባለስልጣናት ውይይት መጀመራቸውን ተከትሎ የኦብነግ ምክትል ሊቀመንበርና ቃል አቀባይ ሙሃመድ ኦስማን አዳኒ ግንባራቸው ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር ንግግር ለመጀመር ዝግጁ መሆኑን ተናገሩ።

ሰኔ 2010 ዓ.ም ፡ በአወዛጋቢ እርምጃ በፕሬዝዳንት ፎርማጆ መንግሥት ለኢትዮጵያ ተላልፎ የተሰጠው የኦብነግ የጦር አዛዥ አብዲካሪም ሙሴ (ቀልቢ ደጋ) ተለቀቀ።

ሰኔ 2010 ዓ.ም ፡ የኢትዮጵያ ካቢኔ አርበኞች ግንቦት 7ን እና ኦነግን ጨምሮ ኦብነግን የሃገሪቱ ፓርላማ ከሽብርተኝነት መዝገብ እንዲያስወጣ የሚጠይቅ የውሳኔ ሃሳብ አቀረበ።

ነሐሴ 2010 ዓ.ም ፡ ኦብነግ የሶማሊያ ፌደራል መንግሥት ግንባሩን የሽብር ቡድን ነው የሚለውን ውሳኔውን ውድቅ እንዲያደርግና ለኢትዮጵያ መንግሥት አሳልፎ ስለሰጠው የጦር አዛዡ በይፋ ይቅርታ እንዲጠየቅ ሃሳብ አቀረበ።

ነሐሴ 2010 ዓ.ም ፡ ኦብነግ ጅግጅጋ ውስጥ የተከሰተውን ግጭት አውግዞ ሁሉም ወገኖች ከኃይል ድርጊት እንዲቆጠቡ ጥሪ አቅርቦ ነበር።

ነሐሴ 2010 ዓ.ም ፡ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድን የሰላም ጥሪን ተከትሎ ወዲያውኑ ተግባራዊ የሚሆን የተናጠል ተኩስ አቁም አወጀ።

ነሐሴ 2010 ዓ.ም ፡ አስር የሚደርሱ የኦብነግ ከፍተኛ ባለስልጣናት በማዕከላዊ ሶማሊያ ጋልሙዱግ በሚባለው ስፍራ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለዋል።

ነሐሴ 2010 ዓ.ም ፡ ኦብነግ ሙስጠፋ ኦማር የሶማሌ ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ሆነው መሾማቸውን ሙሉ ለሙሉ እንደሚቀበለው ገልጾ፤ የኢትዮጵያ መንግሥት በክልሉ ጉዳይ ጣልቃ እንዳይገባ አስጠንቅቋል።

ነሐሴ 2010 ዓ.ም ፡ የቀድሞው የሶማሌ ክልል ፕሬዝዳንት አብዲ ሞሃመድ ኦማር በቁጥጥር ስር መዋል እንደሚደግፍና ይህም ፍትህን ለማስፈን የተጀመረ ትክክለኛ እርምጃ ሲል ገልጾታል።
የኦብነግ መሪዎች

ሊቀመንበር፡ ኡትማን አድም ሙሃመድ ኡማር (ከጥቅምት 2002 ጀምሮ)

ምክትል ሊቀመናብርት፡ አዳኒ ሙሃማድ ኦስማን፣ ኦማር ሙሃመድ ኢስማኤል

የኮምኒኬሽን ኃላፊ፡ ኑር ሁሴን

የአቶ አለነ ማህፀንቱ የፍርድ ቤት ውሎ ከእዮዔል ፍሰሃ

የአቶ አለነ ማህፀንቱ የፍርድ ቤት ውሎ ከእዮዔል ፍሰሃ

  • የፓርቲው የቀድሞ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ተክሌ በቀለን ጨምሮ የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች የምስክርነት ቃላቸውን ሰጥተዋል
  • ተከሳሹም ለፍርድ ቤቱ የተከሳሽነት ቃላቸውን ሰጥተዋል
‹‹ስብሰባን በማወክ ወንጀል›› የተከሰሱት የቀድሞ አንድነት ፓርቲ ማህበራዊ ጉዳይ ኃላፊና ብሔራዊ ምክር ቤት አባል አቶ አለነ ማህፀንቱ፣ በፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 5ኛ ወንጀል ችሎት በመቅረብ መከላከያ ምስክሮቻቸውን አሰሙ፡፡

ችሎቱ ከረፋዱ 5፡00 ሰዓት ላይ የአቶ አለነ ማህፀንቱን መከላከያ ምስክሮች ለማዳመጥ የተሰየመ ሲሆን፤ በችሎቱ የተሰየሙት ዳኛ፣ ተከሳሹ የተከሳሽነት ቃላቸውን እንዲሰጡ ጠይቀዋል፡፡ አቶ አለነ ማህፀንቱም የተከሳሽነት ቃላቸውን በሚከተለው መልኩ ለፍርድ ቤቱ አቅርበዋል፡፡

‹‹ስሜ አለነ ማህፀንቱ ይባላል፡፡ ባለትዳርና የአንድ ልጅ አባት ነኝ፡፡ በትምህርቴ የማስተርስ ዲግሪ ባለቤት ነኝ፡፡ በሙያዬ የተለያዩ ቦታዎች ሰርቼያለሁ፤ በተለያዩ ኮሌጆች ላይ ዲን ሆኜ ሰርቼያለሁ፡፡ በትምህርት ቤቶችም በርዕሰ መምህርነት አገልግያለሁ፡፡ በሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የፖሊሲና ፕሮግራም ኃላፊ ሆኜ ሰርቼያለሁ፡፡ ሀገሬን ወክዬ በተለያዩ ሀገራት በመጓዝ ተከራክሬያለሁ፡፡ 


የሀገሬን ጥቅምም አስከብሬያለሁ፡፡ በፖለቲካ ዘርፍ የ11 ዓመት ልምድ አለኝ፡፡ ለተወካዮች ምክር ቤት እጩ ተወዳዳሪ ሆኖ ከመቅረብ አንስቶ፤ በአንድነት ለፍትህና ለዴሞክራሲ ፓርቲ ብሔራዊ የስራ አስፈፃሚ አባል፣ የብሔራዊ ምክር ቤት አባል እንዲሁም የማህበራዊ ጉዳዮች ኃላፊ ሆኜ እስከተያዝኩበት ቀን ድረስ አገልግያለሁ፡፡ የታሰርኩበትና የተያዝኩበት ምክንያትም በፖለቲካ አመለካከቴ ነው፡፡  

የተቃውሞ ጎራ አባል በመሆኔና እኔም ስታገል የነበርኩት በሀገሬ ላይ ዲሞክራሲን ለማስፈን፤ የፍትሕ ተቋማት ገለልተኛና ነፃ ሆነው አገልግሎት እንዲሰጡ ለማድረግ፤ ዜጎች ያለምንም ምክንያት የማይታሰሩባት ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ፣ ትክክለኛ ፍትህ በሀገሪቱ እንዲሰፍን፣ ትክክለኛ ዲሞክራሲ እውን እንዲሆን ነው፡፡ 

እንደ ተማሩ ወጣቶች ሁሉ ለሀገሬ ሰርቼያለሁ፡፡ በዚህ ስብእናዬ፣ በአካዳሚክ ባክግራውንዴ፣ ባለኝ ማህበራዊ ኃላፊነት አሁን የተከሰስኩበትን ክስ ማለትም አቃቤ ሕግ ያቀረበውን ‹‹አይኤስን ምክንያት በማድረግ መንግስትን በሀይል ለመናድ….›› ወዘት የሚሉ ነገሮች፤ የቀረቡብኝ ባለኝ የፖለቲካ አመለካከት ነው፡፡  

በክሱ ላይ የተዘረዘሩት ነገሮች ሁሉ ባለኝ የፖለቲካም ሆነ የማህበራዊ ኃላፊነቴ ልፈፅማቸው የማልችላቸው መሆኔን አረጋግጬ መናገር እፈልጋለሁ፡፡ በዚህም ምክንያት ሚያዚያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም ከቤቴ በማይታወቁ ሰዎች ታፍኜ ተወስጄያለሁ፤ ከምኖርበት አካባቢ በአራት ደህንነቶች ታፍኜ ተወስጄ ክስ ተመስርቶብኝ፤ በሚያዚያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም በመስቀል አደባባይ በተጠራው ሰልፍ ላይ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ንግግርም ሆነ የሌሎችን ንግግር ለመግታት፣ ‹‹ጉባኤ አውከሃል›› በሚል በወንጀለኛ መቅጫ ህግ 490/3 በመናገሻ ፍርድ ቤት ቀርቤ፤ የአቃቤ ሕግ ምስክር በፖለቲካ ሴራና በተንኮል የተደራጀ በመሆኑ ፍርድ ቤቱ ስላረጋገጠ በነፃ አሰናብቶኛል፡፡

ይህንንም የተከበረው ፍርድ ቤት አምጥቶ ያረጋገጠ ይመስለኛል፡፡ የመናገሻ ፍርድ ቤት በነፃ ካሰናበተኝ በኋላ፤ የኢህአዴግ መንግስት እኔን ማሰር አላማው አድርጎ ስለተንቀሳቀሰ ብቻ በሚያዚያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም ከሶኝ የነበረውን ክስ ሰርዞ፤ ‹‹በሚያዚያ 13 ቀን 2007 ዓ.ም ለቅሶ ቦታ ላይ ተገኝተህ አመፅ ለማነሳሳት ሞክረሃል›› በማለት ክስ አቅርቦብኛል፡፡ ይህ ክስ እኔንም ሆነ ፍርድ ቤቱን የማይመጥን ክስ ነው፡፡ 

‹‹ወጣቶችን አደራጅትህ በሪቼ አድርገህ፣ ወደ መስቀል አደባባይ ወስደሃል›› የሚል ክስ ነው የቀረበብኝ፡፡ የሀሰት ምስክሮች ማለትም፡- የቀበሌ አመራሮች፣ የፎረም አባሎች፣ ሰብስቦ በማምጣት በሀሰት ተመስክሮብኝ እንዲህ አይነት ክስ ሊመሰረትብኝ ተችሏል፡፡ በዚህች ሀገር ላይ የመኖር ዋስትናዬ አልተከበረልኝም፤ እየተከበረልኝም አይደለም፡፡

ስለዚህም የተከበረው ፍርድ ቤት ጭብጥ ማስያዝ የምፈልገው በወቅቱ እኔ ከ2፡30 እስከ 3፡00 ባለው ግምታዊ ሰአት ከጓደኞቼ ጋር ማለትም ከአቶ ግርማ ሰይፉ ቢሮ መገኘቴን ነው፡፡ ‹‹ሙሾ እያወረደ ሲያሳምፅ ነበር›› የሚለው የፈጠራ ክስ በጭራሽ የማይገናኝ ነው፡፡ ከእነዚህው ጓደኞቼ ጋር እስከ ምሳ ሰዓት አብሬ ነበርኩ፡፡›› በማለት የተከሳሽነት ቃላቸውን ለፍርድ ቤቱ ሰጥተዋል፡፡

በፍርድ ቤቱ የተሰየሙት ዳኛ ለአቶ አለነ ማህፀንቱ የተወሰኑ የማጣሪያ ጥያቄዎችን ካቀረቡ በኋላ የተከሳሹን መከላከያ ምስክሮች አድምጠዋል፡፡ 1ኛ ምስክር አቶ ግርማ ሰይፉ ከተከሳሹ ጋር በነበራቸው ቀጠሮ መሰረት ሚያዚያ 13 ቀን 2007 ዓ.ም ከጠዋቱ 2፡30 አካባቢ ቄራ በሚገኘው ቢሯቸው መገናኘታቸውንና ዮናስ ጨርጨር፣ ተብሎ በሚጠራው ሥጋ ቤት አብረው ምሳ መብላታቸውንና እስከ 9፡00 ድረስ አንድ ላይ እንደነበሩ የምስክርነት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ 

በመጨረሻም ስቴዲየም አካባቢ መለያየታቸውን ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡ ከአቃቤ ሕግ በኩል ለተነሱ መስቀለኛ ጥያቄዎችም ምላሻቸውን ሰጥተዋል፡፡ ከፍርድ ቤቱ በኩልም ለተነሳላቸው የማጣሪያ ጥያቄ ምላሻቸውን አስከትለዋል፡፡ በተመሳሳይ 2ኛው ምስክር አቶ ተክሌ በቀለና 3ኛው ምስክር አቶ ስዩም መንገሻ ተመሳሳይ የምስክርነት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡  

አቃቤ ሕግ ለአቶ ተክሌም ሆነ ለአቶ ስዩም መንገሻ መስቀለኛ ጥያቄን አንስቷል፡፡ አቶ ተክሌ በቀለም ሆነ አቶ ስዩም መንገሻ ከፍርድ ቤቱ የማጣሪያ ጥያቄ አልቀረበላቸውም፡፡

የፓርቲው የቀድሞ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ግርማ ሰይፉ፣ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዝዳንቱ አቶ ተክሌ በቀለና የፓርቲ ዋና ፀሐፊ የነበሩት አቶ ስዩም መንገሻ፣ መከላከያ ምስክር በመሆን የምስክርነት ቃላቸውን ለፍርድ ቤቱ ሰጥተዋል፡፡ አቶ አለነ በመከላከያ ምስክርነት አራት ሰዎችን ቢያስመዘግቡም፤ አራተኛ ምስክራቸው የነበሩት የፓርቲው የቀድሞ ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አስራት አብርሃም፣ የምስክርነት ቃላቸውን ሳይሰጡ ቀርተዋል፡፡  

የተከሳሹ ጠበቃ አቶ ሽብሩ በለጠ፣ ‹‹ሶስቱ የመከላከያ ምስክሮች ከሰጡት የምስክርነት ቃል ጋር ተመሳሳይ የሆነ ነገር ሊናገሩ ስለማይችሉ፤ ሶስቱ ምስክሮች በቂ ናቸው፡፡›› በማለት ጠበቃው አስተያየታቸውን መስጠታቸውን ተከትሎ የምስክርነት ቃላቸውን ሳይሰጡ ቀርተዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ የግራ ቀኙን ክርክር ያደመጠ ሲሆን፤ ብይን ለማስተላለፍ ተለዋጭ ቀጠሮ ለጥቅምት 24 ቀን 2008 ዓ.ም ሰጥቷል፡፡

ይድረሰ ለአቶ ታዬ ደንደኣ “እንዴት የሰው ልጅ ሰብዓዊ ክብሩ ወደሚገፈፍበት ጦላይ ይላካል?” ስዩም ተሾመ

ለአቶ ታዬ ደንደኣ

ለአቶ ታዬ ደንደኣ
የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዩች ዳይሬክተር
አዲስ አበባ


ውድ ታዬ፣ የከበረ ሰላምታዬ ይድረስህ! እንደምን አለህ? በእርግጥ ይህን ደብዳቤ በይፋ ከመፃፍ ይልቅ በግል ላናግርህ እንደምችል አውቃለሁ።

ነገር ግን ይህን ለማድረግ ውስጤ አልፈቀደም። ምክንያቱም በማዕከላዊ እና ሦስተኛ እስር ቤቶች ውስጥ ብዙ ብዙ ነገሮችን ተጫውተናል። በእውነቱ ከአንተ ጋር መታሰር ትምህርት ቤት እንደ መግባት ነው። ከአንተ ብዙ ነገር ተምሬያለሁ።

በተለይ ደግሞ በሀገራችን ፖለቲካዊ ስርዓት ላይ ሥር-ነቀል ለውጥና መሻሻል ለማምጣት፣ በዚህ የዜጎች መብትና እኩልነት የተረጋገጠበት ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለመገንባት ቀዳሚው ተግባር ፍትህ እና የህግ የበላይነት ማረጋገጥ አለበት የሚል ፅኑ እምነት እንዳለህ አውቃለሁ።

ባለፈው የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዩች ዳይሬክተር በመሆን ስትሾም ሙሉ በሙሉ ደስተኛ ያልሆንኩት ለዚህ ነው። ምክንያቱም ገና እስር ቤት እያለን “ታዬ አንተን ማየት የምፈልገው የኦሮሚያ ፍትህ ቢሮ ኃላፊ ወይም ደግሞ የፌደራል ጠቅላይ ዋና አቃቤ ሆነህ ነው” ብዬህ እንደነበር ታስታውሳለህ።

በእርግጥ እስር ቤት ውስጥ የተወያየንባቸውን ጉዳዮች በሙሉ አንድ በአንድ ታስታውሳለህ ብዬ አልጠብቅም። ነገር ግን ዕምባዬን እያፈሰስኩ በዝርዝር የነገርኩህን ነገር ግን የምትረሳ አይመስለኝም።

በማዕከላዊ እስር ቤት ከነበርኩበት ጣውላ ቤት ወደ “09” ወይም ሸራተን ተዛውሬ እንደመጣሁ “እስኪ ስለ ጦላይ ንገረኝ?” ብለህኝ ነበር። በ2009 ዓ.ም ከተለያዩ የኦሮሚያ አከባቢዎች የመጡ ከአምስት ሺህ የሚበልጡ ሰዎች “ጦላይ” በሚባል ምድራዊ ሲዖል ውስጥ ምን ዓይነት ግፍና በደል እንደ ተፈፀመባቸው በዝርዝር ነግሬህ ነበር።

ጦላይ ውስጥ ስለሆነው ነገር መናገር አልሻም። ጦላይ ውስጥ የታዘብኩትን አሰቃቂ እውነት ተመልሶ ማሰብ፣ በእኔ ላይ የደረሰው በደልና ሰቆቃ በፍፁም ማስታወስ አልሻም።

በዚያ የተረገመ ቦታ ያየሁትን ግፍና ሰቆቃ ስናገር ነፍሴ ትሰቃያለች፣ አንደበቴ በሲቃ ይዘጋና መናገር ይሳነኛል። ስለዚህ በቃላቶች ፋንታ ዕምባዬ ይፈስሳል። በውስጤ ታፍኖ ያለው መከራና ስቃይ በዕምባ መልክ ገንፍሎ ይፈስሳል።

አንደበቴ በሲቃ ተሞልቶ የጦላይን ስቃይና ሰቆቃ በዕምባዬ የምነግረው በጣም ለምቀርበው ሰው ብቻ ነው። ከዚህ ውስጥ አንዱ ታዬ አንተ ነህ። ይህን የነገርኩህ ደግሞ እንደ ጓደኛ ብቻ ሳይሆን ጦላይ ውስጥ ያንን አሰቃቂ ተግባር የፈጸሙ የኦሮሚያና ፌደራል ፖሊሶችን ለፍርድ ታቀርባለህ የሚል ፅኑ እምነት ስለነበረኝ ነው።

ምክንያቱም በወቅቱ የኦሮሚያ ፍትህ ቢሮ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ስለነበርክ ብቻ ሳይሆን በፌደራል ደረጃ ትልቅ ቦታ እንደምትደርስ አውቃለሁ።

ከሁሉም በላይ ደግሞ “እዚህ ሀገር ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለመገንባት ቀዳሚው ተግባር ፍትህ እና የህግ የበላይነት ማረጋገጥ ነው” የሚል ፅኑ እምነት እንዳለህ አውቃለሁ።

ይሁን እንጂ አንተ የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ ኃላፊ ሆነህ ሳለ ወደ አንድ ሺህ አራት መቶ (1400) የአዲስ አበባ ወጣቶች ወደ ጦላይ ተወስደዋል። እስካሁን ድረስ በዚህ ጉዳይ ላይ ብዙ ነገር ማለት አልፈልግም ነበር። ምክንያቱም አንደኛ፡- ውጪ ሀገር ስለነበርኩ በጉዳዩ ዙሪ ሙሉ መረጃ አልነበረኝም፣ ሁለተኛ፡- ይህ ተግባር በዕውን ይሆናል ብዬ ማመን አልቻልኩም።

ጦላይ ወታደራዊ ካምፕ ነው። ለወታደራዊ ስልጠና ከሚላኩ ሰዎች በስተቀር ማንም ሰው ወደዚያ ቦታ መሄድ የለበትም።

ምክንያቱም ሰዎች ወደ ጦላይ የሚወሰዱት ለሰው ልጅ ክብርና ርህራሄ የሌላቸው ፍፁም ጫካኝ የሆኑ ፖሊሶችና ወታደሮች፣ ከዓለምና ከኢትዮጵያ ህዝብ እይታ ተሰውረው፣ መንግስትና ህግ በሌለበት፣ የዜጎችን ሰብዓዊ ክብር ለመግፈፍ እንዲያመቻቸው እንደሆነ እኔ በተግባር አይቼዋለሁ።

ውድ ታዬ… የተጠቀሱት የአዲስ አበባ ወጣቶች ወደ ጦላይ እንዲላኩ አድርገሃል ብዬ እየወቀስኩህ አይደለም። በእርግጥ እንደ የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዩች ኃላፊ ጉዳዩ አንተን ይመለከታል።

ይሁን እንጂ እነዚህን ወጣቶች በራስህ ጦላይ ማስገባት ሆነ ማስወጣት እንደማትችል አውቃለሁ። ምንአልባትም በዚህ ጉዳይ ላይ ምንም ማድረግ አትችል ይሆናል። ነገር ግን፣ ቁስሌ ሳይሽር፣ ዕምባዬ ሳይደርቅ እንዴት ሰው ወደ ጦላይ ይላካል?


ብዙ ምክንያት ልትጠቅስልኝ፣ ብዙ ነገር ልትነግረኝ እንደምትችል አውቃለሁ። የምትነግረኝ ነገር ግን ስለ ጦላይ የማውቀውን፣ እዚያ የተደረገውን እና የሚደረገውን ነገር አይቀይረውም። የሰው ልጅን ወደ ምድራዊ ሲዖል መላክ በምንም አግባብ፣ እንዴትም ሆኖ ተቀባይነት ሊኖረው አይችልም።

እንዴት ታዬ?? እንዴት እንዲህ ይደረጋል? እንዴት የሀገር ልጅ ወደ ጦላይ ይላካል? እንዴትና ለምን በእኛ ላይ የደረሰው በአዲስ አበባ ልጅ ላይ ይደገማል? ታዬ የክፉ ቀን ወዳጄ… እንዴት የሰው ልጅ ሰብዓዊ ክብሩ ወደሚገፈፍበት፣ ወደዚያ የተረገመ ቦታ ይላካል???? እንዴት……